Skip to content

Amharic Quran

ከመሞትህ በፊት ቁርአንን አንብብ! (Read the holy Quran before you die!)

  • Amharic Quran
    • ድጋፍ ያድርጉልን
  • Blog
    • ቁርአንን እንረዳው
    • Quran in Oromigna

የእስልምና ታሪክ መበደል

Posted on May 1, 2025 By Amharic Quran 1 Comment on የእስልምና ታሪክ መበደል
የእስልምና ታሪክ

የእስልምና ታሪክ መበደል

መግቢያ
የእስልምና ታሪክን ለማጠልሸት የቻሉ ክፍሎች

ኢማሙ አል-ጠበሪይ ታሪክን ከሰበሰቡበት እለት ጀምሮ የእስልምናን ታሪክን አስቦ የሚነሳበት አዋቂ ባይጠፋም አንዳንዱ አደገኛነቱን ባለመገንዘብ ሳያጣራ ያገኘውን ሲጽፍ ሌላው ደግሞ አስቦበት እንደ ራፊዷ ያሉና ሌሎችም ለእስልምና ቅን መንፈስ የሌላቸው ተንኮለኛች በወገንተኝነት በእስልምና ታሪክ ውስጥ ያስገቡትን ቅጥፈት ከአል-ጠበሪ የታሪክ መጽሐፍ በመውስድና እንዲሁም ከተመሳሳይ መጻሕፍት በደካማ መረጃ የተደገፈ ቅጥፈትን ለአንባቢ እውነት አስመስለው ለማቅረብ ችለዋል።

እንደ ምእራባውያን ያሉ ጸሐፊዎች ደግሞ ስለእስልምና ታሪክ ለመጻፍ በሚፈልጉበት ጊዜ ታሪኩን ከራሳችን የታሪክ መጻሕፍት በመውሰድ ታሪካችንን በርዘውና ከልሰው ይጽፉልንናል ። እነዚህም ምእራባውያን በኦሬንታሊስት ስም ሲታወቁ አብዛኞቹ የእስልምና ታሪክን የሚያጎድፈውን በመምረጥ ከእነሱ የመነጨ ታሪክ ጋር ቀላቅለው ያቀርቡታል። ኦሬንታሊስት የሚባሉትም ከምእራብ የፈረንጅ አገሮች ወደ ምሥራቅ የአረብ አገሮች ሄደው ስለ እስልምና ታሪክ የሚያጠኑ ሲሆኑ ብዙዎቹ በታሪክ አጻጻፋቸው ላይ ታማኝነት የሌላቸው ሆነው ይታያሉ። በተጨማሪም ኦሬንታሊስቶች የራሳቸውን አስተያየት በመጨመር የሚጽፉት የተሳሳተ ታሪክ በየገበያው በየቋንቋው ታትሞ ይሸጣል። የኦሬንታሊስት የተሳሳተ የእስልምናን ታሪክ መጻፍ ብቻ ሳይጎዳ በዘመናችን የበለጠ አስከፊ የሆነው ነገር በአንዳንድ ሙስሊም ናቸው የተባሉ ጸሐፊዎች የሚታየው ምእራባውያን ከሚጽፉት መጽሐፍ እንደ መረጃና ዋቢ አድርገው በመውሰድ ታሪካችንን ለማጠልሸት መቻላቸው ነው።

ከሊፋ ዑስማን ብን ዓፋንን (ረዐ) ገድለው በሶሓባዎች (ረዐ) መካከል የእርስበርስ ጦርነት እንዲነሳ ለማድረግ የቻሉ በሙስሊም ስምና በሙስሊሞች መካከል ተሰግስገው የሚገኙ የኢስላም ጠላቶች እስከ አሁንም ድረስ ታሪካችንን በማጠልሸት ከሶሓባዎች (ረዐ) ጋር እንድንቃቃር ለማድረግ ሞከራቸውን አላቋረጡም። ከነዚህ አጥፊዎች መካከል ዋነኞቹ እንደ ራፊዷዎች ያሉ በቅጥፈት ከሚጽፉት ታሪክ ለምሳሌ ብናቀርብ እንደ እናታችን ዓኢሻ (ረዐ) ያሉትን በዓልይ አቢ ጣሊብ (ረዐ) ላይ ጦርነት አስነስተዋል በማለት የታሪክን መልክ ለመቀየር ችለዋል።

እንዲሁም የዓልይና (ረዐ) የሙዓውያ (ረ.ዐ) ጦርነት ምክንያት የነበረው የዑስማን (ረዐ) ገዳዮችን እንዳልሆኑ አድርገው በማጥፋፋት በመካከላቸው የሥልጣን ሽሚያ እንደነበርና ሙዓውያ (ረዐ) ከዓልይ (ረዐ) ሥልጣናቸውን ለመንጠቅ የተደረገ ጦርነት አስመስለው በማስወራት መንስኤው የአሚር አል-ሙእሚኒን የዑስማን (ረዐ) በአመጸኞች መገደል እንዳልሆነ በማስመሰል ፍጹም የታሪክን መልክ በመቀየር ብዙሃኑን ለማሳመን ችለዋል።

ይህን ያደረጉበት ዋነኛ ምክንያትም የአመጸኞቹን ተንኮል ለመሸፈንና የዑስማን (ረዐ) ገዳዮችን የፊትና እሳት ጫሪዎች መሆናቸው እንዳይታወቅ ለማጥፋፋት ያደረጉት ሴራ እንጅ ዓልይን (ረዐ) ለመደገፍ ያደረጉት ቅጥፈት ፍጹም አልነበረም ። እንዲሁም በዓልይ (ረዐ) በሙዓውያ (ረዐ) የውጊያ ማቆም ስምምነት ምክንያት ከሁለቱም ወገን ለአስታራቂነት የተመረጡ ሶሓቦችን ስም በማጥፋት አንዱን ሶሓብይ ጮሌላና አታላይ ሲያስመስሉ ሌላውን ቂላቂልና በቀላሉ የሚታለል በማስመሰል እርቁ እንዲፈርስ ያደረጉ አመጽኞቹ እንዳልሆኑ አድርገው ብዙዎቻችንን ሊያሳምኑ ችለዋል።

ይህን የመሳሰለ ልዩ የሆነ ቅጥፈት በመቅጠፍ ታሪክን በመበረዝ ሰላምና እርቅ እንዳይሰፍን ለማደፍረስ ሆን ተብሎ ታስቦበት ከዑስማን (ረዐ) መገደል በኋላ ያለው ታሪካችን ብዙ ብልሽት የገባበት በመሆኑ በብርቱ ጥንቃቄና በቂ መረጃዎች እየተመረጡ ለማስተካከል በዘመናችን ሙስሊሞች የታሪክ አዋቂዎች ጥረት እያደረጉ ጥሩ ውጤት እያሳየ ነው። ይህን ጥፋት ያዘለ ታሪክ ግን እስካሁንም በሺዓዎች በኩል ከፍተኛ ክንክን ተሰጥቶት በየሚዲያው በየመጻፍሕፍቱ በየሑሰይንያው (የሺዓዎች መሰብሰቢያ ሌሎች የሱና ተከታይ ሙስሊሞች የማይቀላቀሉበት ሶሓባዎች በየደቂቃው የሚሰደቡበትና የሚረገሙበት ቦታ) በየጊዜው እንደ ከቁርአን የበልጥ ይነበባል።

በተለይ የመጀመሪያዎቹ የፊትና አባቶችና የኢስላም ጠላቶች የነበሩትን የሠሩትን እርኩስ ተግባር ሁሉ በመሸፈን እንዲሁም ጀብዱ ሥራ የሠሩ አድርገው በማጋነን እነሱን ለማወደስ ራፊዷዎች የሚያፍሩበት ነገር ሆኖ አልተገኘም። በአንጻሩ ግን የነብዩ (ሶ.ዐ.ወ) ሶሓቦችን (ረ.ዐ) በማዋረድና በማናናቅ ያለ አንዳች ፍራቻ ሲቀጥፉ ይታያሉ ።

በዚህ አይነት ራፊዷዎች በቅጥፈት ያስገቡትን የታሪክ ጠለሸት ብዙ ጸሐፊዎች ሳያጣሩ የጻፉት በአህለል ሱና ኪታቦች ውስጥ በመገኘቱ ብዙዎቻችንን እውነተኛ ታሪክ መስሎ ሊያሳምነን ችሏል ። ራፊዷዎች ታሪክን በማዛወር እኛን ለማሳመን ከሚሞክሩበት አንዱ የሑሰይን ብን ዓልይ ብን አቢ ጣሊብ (ረዐ) መገድልን የሚያወሳውን ታሪክ በመቀያየር ነው።

ራሳቸውን የሑሰይን (ረዐ) ደጋፊዎች በማድረግ የሱና ተከታዮችን ደግሞ ገዳዮች እንደሆኑ አድርገው በማስወራታቸው በማናቀው ነገር በየትኛውም ዘመን በማንኛውም ሺዓ ነኝ በሚሉ ሰዎች አይን በጥላቻ እንድንታይ አድርጎናል።

ነገር ግን ትክክል ያልሆነ ታሪክን በመከተል ለሑሴን (ረዐ) መገደል ምክንያት አህለል ሱናዎች እንደሆኑ አድርገው እንደጠላት ሲያዩ ዓልይን (ረዐ) የገደለ ከራሳቸው ሺዓ (ደጋፊ ወይም ተከታይ) በነበረ በከዋሪጅ እጅ መሆኑን እምብዛም የቆጫቸው አይመስልም ከዋሪጆችም የዓልይ (ረዐ) ሺዓ እንደነበሩ ፍጹም ለመጥቀስ ፍጹም አይሞክሩም።

በተለይም ራፊዷዎች ሃቅን እንደሚደብቁ ልናውቅ የሚያስችለን ነገርና የኢስላም ጠላት የሚያስመስላቸው በዑስማን (ረዐ) ገደላ ሴራ ተሳትፈው የነበሩ ወንጀለኞች የነበሩ እንደ አል-አሽተርና ሙሐመድ አቡ በከር ወዘተ.. ያሉትን ቀንደኞች የፊትና እሳት ቆስቋሾች የነበሩትን በመልካም ነገር ካልሆነ በስተቀር ማንም ሰው በመጥፎ እንዲያነሳቸው ያለመፍቀዳቸው ነው።

በአንጻሩ ግን የከሊፋ ዑስማን (ረዐ) በግፍ መገደል እንኳንና ሊቆጫቸው ዑስማንን (ረዐ) ጥፋተኛ ለማድረግ ብዙ የቅጥፈት ታሪኮችን ፈብርከው ይገኛሉ። ከዚህም አልፈው ዑስማንን (ረዐ) የገደሉ ሶሓቦች ናቸው ለማለት አላፈሩም። ይባስ ብሎ እናታችን ዓኢሻን (ረዐ) የዑስማን (ረዐ) ገዳዮች ተባባሪ እንደነበሩ አድርገው የሚያስወሩ የአላህ ፍራቻ የሌላቸው የራፊዷዎችን ተንኮል በመረጃ ለአንባቢዎች ኢንሻአህ እናቀርባለን።
ይቀጥላል

በአህመድ ሰ. አል-ከሽዓን የተዘጋጀ (https://www.facebook.com/islamawitarik )

Tags: የእስልምና ታሪክ የእስልምና ታሪክ መበደል

Post navigation

❮ Previous Post: Quran in Afaan Orormo

One thought on “የእስልምና ታሪክ መበደል”

  1. 4 says:
    July 9, 2026 at 5:08 pm

    4

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

  • Amharic Quran
  • Blog
  • Amharic Quran
  • Blog

Copyright © 2026 Amharic Quran.

Theme: Oceanly Green by ScriptsTown